Thursday, October 30, 2014

ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ፀልዩ



              ፀልዩ
                             ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ፀልዩ    ማቴ.26÷41
      ራሱ ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ በቀጥታ የተናገረው መለኮታዊ ትዕዛዝ ነው ፡፡በሀዲስ ኪዳን መፅሐፍት ውስጥ ከታወቁት ስድስቱ ቃላተ ወንጌል በተጨማሪ ከ600 በላይ ቀጥተኛ የቅድስና ትዕዛዛት አሉ ፡፡ ለምሳሌ፤- ሊደረግብህ የማትፈልገውን በሰው ላይ አታድርግ ፤ ፁሙ ፣ ፀልዩ ፣ ክብር ለሚገባው ክብር ስጡ ፣ባላጋራህን እንደ ራስህ ውደድ ፣ ካባህን ከወሰደ መጎናፀፊያህን ጨምርለት ወዘ.ተ እነዚህ ቀጥተኛ ትዕዛዛት ህግ ባይሆኑም እንኳን ከህግ የተሻለ ሰዎችን ወደ እግዚአብሔር ሀሳብ የሚያቀርቡ የቅድስና መንገዶች ናቸው ፡፡ ሌሎቹን ለጊዜው ተወት እናድርጋቸውና ወደ ዋናው የዛሬው ትኩረታችን ወደ ፀሎት እንመለስና አንዳንድ ነገር እንገንዘብ ፡፡
      የዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነውን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በጥልቀት ስንመረምር የፀሎትን ኃይል፤ጉልበት፣ መፍትሄ ሰጭነትና ሁለንተናዊ መንፈሳዊ መሳሪያነት ፍንትው አድርጎ ያሳየናል ፡፡ ጊዜው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመስቀሉ 18 ስዓት ቀደም ብሎ ነው ሁሉም ነገር ተጠናቋል የቀረው አንድ ነገር ብቻ ነው የጌታ ተላልፎ መሰጠት ፡፡ በዚህ አስጨናቂ ጊዜ በሞትና በህይወት መካከል የሰከንድ ሽርፋፊ ብቻ ቀርቶ እንኳን ጌታ ይፀልይ ነበር ሐዋርያትንም በርትተው እንዲጸልዮ አበክሮ አሳስቧቻው ነበር ያውም በትጋትና ያለማቋረጥ ፡፡ ይህ ማለት ፀሎት በከፍኛ ትጋት የሚፈፀምና የማይቋረጥ ለነፍስ ከኦክስጂን በላይ አስፈላጊ ነገር ነው ማለት ነው ፡፡ የሚያምን ሰው ከአምላኩ የሚገናኘው በፀሎት ነው እግዚአብሔር በቃሉ በኩል ይናገራል አማኝ ደግሞ በጸሎት ይመልሳል ፡፡ፀሎት የለም ማለት ግንኙነት ተቋርጧል ማለት ነው ፡፡ህይወት ከሚሰጠው የተለየ ደግሞ ህያው መሆን አይችልም ፤ አሳ ከባህር ከወጣ ፤ ቅርንጫፍ ከዛፉ ከተለየ ፤ አምፖልስ ከጀነሬተሩ ጋር የሚያገናኘው ከሌለ ምን ህይወት አለው ምንም፡፡ ስለዚህ ፀሎት በስህተት እንኳን የምናቋርጠው ነገር አይደለም ፡፡ ስዓት ቆጥረን እንደ ስራ ወይም መከራ ሲበዛብን እንደማምለጫ የምንጠቀመው የእንቅስቃሴያችን አንድ ክፍል ሳይሆን በእያንዳንዱ የህይወት መንገድ እግዘአብሔርን እያከበርን የምንኖርበት የአምልኮ መገለጫ ነው የህይወት ዘመን ሙሉ መንፈሳዊ ለምምድ ነው፡፡ እግዚአብሔርን በእያንዳንዱ የሰከንድ ሽርፍራፊ ማሰብ ፀሎት ነው ፡፡ ታላቅ ፀሎትም ነው ፡፡ የቀደሙት የእግዚአብሔር ሰዎችን ህይወት ስናጠናም በፀሎት እጅግ ድንቅ እንዳደረጉ እናውቃለን ፤ ጌታም በወንጌል በፆምና በፀሎት ምን ያህል ኃይል እንደሚደረግ አጋንንትንም ማሸነፍ እንደሚቻል አስተምሮናል ፡፡ ማቴ.17÷21
      በእግዚአብሔር ፊት ለጸሎት በምንቆምበት ጊዜ የግድ ሊጤኑ የሚገባቸው ነገሮች አሉ ፡-
1.   በመንፈስ ሆኖ መፀለይ ፡- ፀሎት ድጋም አይደለም ፡፡ ፀሎት የመንፈስ መነጠቅ ነው ፤ ጸሎት ከእግዚአብሔር ጋር መገታኘት ብቻ አይደለም መነካካትም ጭምር እንጅ፡፡ ፀሎት ከነፍስ የሚከፈል ወደ ተለየ ዓለም የሚነጥቅ ልዩ ጣዕም ያለው በስጋ ሀሳብ ሊገለጥ የማይችል የተለየና ከመንፈስ ቅዱስ የሆነ መለኮታዊ የግንኙነት መስመር ነው፡፡ አንድ መጽሐፍ ገልጦ ከመግቢያው እስከ ማሳሰቢያው ማንበብ ፀሎት አይባልም ፡፡ አበው የዘንድሮ ፀሎት አይን ፊደል ይነዳል ልቤ ቤት ያሰናዳ ነው  እንዲሉ፡፡በጸሎት ጊዜ ሀሳብን መሰብሰብ፤መመሰጥ፤በተቻለ መጠን ከጸሎት አስቀድሞ በጸሎት መሀል እየተመላለሱ ለሚረብሹ ሀሳቦች ለጊዜውም ቢሆን መፍትሄ መሰጠት ያስፈልጋል፡፡
2.         በእምነት ሆኖ መፀለይ ፡- አምናችሁ የምትፀልዩበትን ሁሉ ትቀበላላችሁ ፡፡ የምንፀልየው ተስፋችንን ሳይሆን እምነታችንን ነው ፡፡ ምንም ነገር ቢሆን ስለሰጠኸን፣ ስላደረክልን እንላለን እንጂ ስለምታደርግልን ብለን ቀጠሮ አንይዝም ፡፡ በቃ ስንፀልይ አባታችን  ሰምቶናል መልሱን ለልጆቹ መስጠት ደግሞ ያውቅበታል ማቴ 6፤8-9፡፡ በፀሎት የጠየቅነውን አምነን እርግጠኛ የሆንበትን ነገር ባንቀበልስ ከተባለ እርሱማ ስለማይጠቅመን እግዚአብሔር የከለከለን ነው ፡፡ ይኸ ደግሞ ከመቀበል እኩል ነው ፡፡ በነገራችን ላይ ልመና በፀሎት ክፍል ውስጥ በጣም ትንሹና የግድ አስፈላጊ ያልሆነው ክፍል ነው ፡፡ የለመነውን የግድ ማግኘት አለብን ብለን ከእግዚአብሔር ጋር ሙግት ከገጠምን ግን ብንቀበል እንኳን ፍቃዱ ሳይሆን የወሰድነው ነገር ያጠፋናል ፡፡ 1ኛ ሳሙ.8÷7 እንደፈቃድህ ይሁን ብሎ ምንፀለየውም ለዚህ ነው ፡፡ለሚያምን ሁሉ ይቻላል ለማያምን ደግሞ ምንም አይቻልም፡፡
3.          በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መፀለይ ፡- ጌታ በወንጌል በስሜ አልፀለያችሁምና አልተቀበላችሁም ብሏል ፡፡ ፀሎት ሁል ጊዜም ወደ ሥላሴ መንግስት ይቀርባል ፤ አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስም በዙፋናቸው የእያንዳንዱን ልመናና ፀሎት ያደምጣሉ፣ ይፈርዳሉ፣ ይመግባሉ፣ ያስተዳድራሉ … አማኞችም የዳኑት በሥላሴ መንግስት ውሳኔ ስለሆነ ( በእርሱ ፈቃድ ፣ በአባቱ ፈቃድ ፣ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ) መጥቶ አዳነን እንዲል ፤ በዚህ ድህነት የእግዚአብሔር ልጆች ሆነዋልና በዳኑበት ስም ፣ በዳኑበት ደም ፣ በዳኑበት አምላክ ይፀልያሉ ፡፡በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መፀለይ ማለት  ክርስቶስ የከፈለው የማዳን ዋጋ ዛሬም ህያው ነው ብሎ ማመን ፣ ወደ ቆምንበት ወደዚህ ፀጋ እንዴት እንደባን ማስታወስ ወይም አሁን እንኳን ወደ እግዚአብሔር ለመፀለይና በፊቱ ለመቆም  የቻልነው ጥል ስለተወገደ  ነውና ይህንን ጥል ያስወገደልንን ጌታ እያሰብን ባገኘነው የልጅነት ክብር አባ አባት እያልን እንፀልያለን ዮሐ 16፤26-27 ፡፡ ጌታ ራሱ አብ በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ ይሰጣችኋል እንዳለ ዮሐ 15፤16 ፡፡ በእለተ አርብ መስዋዕት በሆነ ጊዜ፣ ራሱም መስዋዕት አቅራቢ ብቻ ሳይሆን ተቀባይም እንደነበር ከእግዚአብሔር ጋር በታረቅንበት በክርስቶስ ስንፀልይም በስሙ የተፀለየውን ፀሎት በሥላሴ መንግስት አንዱ ወልድ ከመንፈስ ቅዱስና ከአብ ጋር ጸሎታችንን ይቀበላል ፡፡ ወደ ሥላሴ የደረስነው በክርስቶስ  ነው እለት እለትም የምንደርሰው ከክርስቶስ የተነሳ ነው፡፡                                                                                                                             

ፀሎት አራት መሠረታዊ ክፍሎችን ያጠቃልላል
      ሊቃውንት እንደሚሉት ብዙ ጊዜ ከመለመን አንድ ጊዜ ማመስገን ይሻላል ፡፡ በመሆኑም የመጀመሪያው የፀሎት ክፍል ምስጋና ነው ፡፡ የምስጋና ኃይል የትኛውንም የተዘጋና የተቆለፈ ነገር መክፈት ይችላል ፡፡ እግዚአብሔር ከሁሉም በላይ በአመስጋኞች እጅግ ደስ ይለዋል ፡፡ በሁሉ ስለ ሁሉ አመስግኑ ተብሎ እንደተፃፈ ፡፡ አማኞች በፀሎታቸው ጊዜ ሊዘነጉት የማይገባውና ዋነኛው ክፍል የምስጋና ክፍል ነው ፡፡ ምስጋና አራት የተለያዩ ክፍሎች ይኖሩታል ፡-
1. እግዚአብሔርን ማመስገን ፤-ስለ ፍጹም አንድነቱ፤ስለመለኮታዊነቱ ፣ ስለ ሀልወቱ ፣ ስለ ታላቅ ችሎታው ፣ ስለ ማይወሰን ኃይሉ ፣ እጅግ ግሩም ስለሆነው ባህሪው ማመስገን ፣ ለምሳሌ፡- የዘላለም አባት  ጌታ እግዚአብሔር አምልካችን ሁሉን ስለያዝክ ፣ ሁሉን ስለምታኖር ፣ የሚታየውንና የማይታየውን ስለፈጠርክ ፣ ከሀረፃንነታችን ጀምሮ ስለጠበቀን ፣ በብዙ በረከት ስላሳደከን ፣ እጅግ ሩህሩህና ይቅር ባይ ፣ አፍቃሪና የዋህ ስለሆንክ ፣ ስለማይነገረው ስጦታህ ሁሉ እናመሰግንሀለን ፡፡ደገሞም አባትነትህን እንድንረዳ አምላክነትህን እነድናውቅ ስለረዳህን አንተን በማመን ወደመገኝ ህይወት ስለደረስከን አንተን በመስማት ወደሚገኝ ረፍት ስለመራሀን እናመሰግነሀለን ፡፡ልንል እንችላለን ፡፡
        2.የሥላሴን መንግስት ማመስገን ፡- መንግስትህ ትምጣ ብለን መጸለይ እንዳለብን ክርስቶስ አስተመሮናል፤፤ የእግዚአብሔር መንግስት ማለት ሁለንተናዊ የእግዚአብሔር አስተዳደር ማለት ነው ይህ መለኮታዊ መንግስት በሶስት አካላት በአንድ ዘላለማዊ ስልጣን የሚመራ ነው፡፡ስለሆነም ይህንን ተወዳጅ አምላክ ታለቅ ጌታ ዘላለማዊ ንጉስ ከላይ በጥቅል እግዚአብሔር ያልነውን አምላክ በተለየ አካሉና ባህሪው ማመስገን አስፈላጊ ነው፡፡
 ለምሳሌ ፡-    .  የጌታችንና የመድሃኒታችን አባት እግዚአብሔር አብ አምላካችን እናመሰግንሀለን፤- ከስጦታ በላይ የሆነ ስጦታ የተወደደ ልጅህን ስለ ኃጢያታችን ይቅርታ ይሞትልን ዘንድ ስለሰጠኸን ፣ በአንድ ልጅህ ጨክነህ እኛን ሞት የሚገባንን ስላዳንከን፤ መንግስትህ ለዘላለም ስለሆነች፤ ለግዛትህም ልክና ወሰን ስለሌለው ፡ የማትተረጎም፡ የማትተረክ፣ የምትደነቅና የምታስገርም፤ የምትወደድና የምትፈቀር ስለሆንክ ከእኛ በላይ ለእኛ ስለምታስብ እንደ አይን ብሌን ስለምትጠነቀቅልን እናመሰግንሀለን፡፡ልንል እንችላለን፡፡
·         ጌታችን መድሀኒታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናመሰግንሃለን፣ ስለነዚያ ችንካሮች ፣ እየተራብክ ስላጠገብከን ፣ እየተጠማህ ስላጠጣኸን ፣ ራቁትህን ሆነህ በፀጋ ስላለበስከን ፣ ወደ መንግስትህ ስላፈለስከን ፣ በተሰበረው በኩል ሁል ጊዜ ስለምትቆምልን ፣ እናትም አባትም እህትም ወንድምም ሆነህ ስለደገፍከን ፣ በደምህ እየጋረድህ የሰይጣን ምክሩን እያጠፋህ በህይወት እንድቆም ዛሬን እንዳየው ስለረዳህን እናመሰግንሃለን፡፡ ልንል እንችላለን ፡፡
·         ጌታ መንፈስ ቅዱስ ሆይ ስለ አምላክነትህ ፣ ስለ አጽናኝነትህ ፣ ስለ ምህረትህ ፣ እናመሰግንሃለን ፤ የኃይል መንፈስ፤የእውቀት መንፈስ፤የእውነት መንፈስ ፣ የጽድቅ መንፈስ ፣ የይቅርታ መንፈስ ፣ የፍቅር መንፈስ ፣የህይወት መንፈስ፤የእግዚአብሔር መንፈስ፡፡ ቤተክርስቲያንን ለሙሽራው ኢየሱስ ሰርግ የምታዘጋጅ፣ የምታስውባት ፣ የምታነፃት አንተነህና ክብር ይገባሀል ፡፡ በእውነት የቀደሙትን አባቶች ስላገዝክ ፣ አለማትን በወንጌል እንዲከድኑ ፣ የአላውያንን መከራ እንዲታገሱ እውቀትና ጥበብ ፣ ጽናትና ድፍረት ፣ ጥበብና ትምክህት ስለሆንካቸው እኛንም በነገር ሁሉ እንዲከናወንልን ስለረዳኸኝ አመሰግንሀለሁ፡፡ ልንል እንችላለን ፡፡
                  3.እግዚአብሔርን ስለ ትድግናው  ( ስለ ጥበቃው ) ማመስገን ፡- ለምሳሌ ፡- ጌታ ሆይ ዛሬ በህይወት መኖሬ ይገርማል ፡፡ ስታመም አልጋየን አንጥፈህ ፣ ስወድቅ ቀድመኸኝ ወድቀህ ፤ የማይወጣውን እንድወጣ ጉልበት ሆነህ አኖርከኝ ፣ ከንፈሬን በእልልታ ፤ አፊን በምስጋና ሞላህ ፣በአውሎና በወጀብ አሳለፍከኝ ፣ የተቆረጠውን ሁሉ ቀጥለህ ፀሐይ አወጣህልኝ ፡፡ መከራየን ሁሉ እንዳለፈው ክረምት አሳለፍከው ተመስገን ፡፡ ባእድን ዘመድ ፣ ክፉውን መልካም፣ እያደረግህ ስንት ጊዜ ረዳኸኝ ስንት ጊዜ አስመለጥከኝ፣ ስንት ጊዜ አሻገርከኝ ፣ስንት ጊዜ ተከራከርክልኝ፣ ስንት ጊዜ አሸነፍክልኝ፣ ስንት ጊዜ ተመካሁብህ የኔ ጌታ ሲያልፍ ቀለቀል ይመስላል እንጅ አንተ ከእኔ ጋር ባትሆንማ ያ ሌሊት አይነጋም ነበር ፤ አባቴ፣ መድሀኒቴ ፣ ወዳጅ ፣ ከፍ በልልኝ፡፡ ልንል እንችላለን ፡፡
                    4.እግዜአብሔርን ስለ ስጦታው ሁሉ ማመስገን ፡- ለምሳሌ ፡- ሁሉ ካንተ ፣ሁሉ ባንተ፤ ሁሉ ለአንተ ነው ፡፡ ከእኔ የሆነ ምንም ነገር የለም ሥራየን የሰራኸው ፣ ብርሃኔን ያበራኸው አንተነህ ፣ የሚበላና የሚጠጣውን ፣ ትዳርና ልጆችን ያገኝሁት ካንተ ነው ፣ እንዲህ የተትረፈረፈልኝ ቤቴ ስለገባህልኝ ነው ፣ ቆጥሬ የማልጨርሰውን የተቀበልኩት ካንተ ነው ፣ ተመስገንልኝ ፡፡ ካንተ ያልሆነ ምን አለ፣ በህይወቴስ ካንተ ሌላ እንዲህ አረገልኝ የምለው ማን አለ ? ክብሩን ሁሉ ጠቅልለህ ውሰድ ፣ የሰጠኸኝ ሁሉ ለአንተ ክብር ይሁንልኝ ፡፡ ባበዛህልኝ ነገር እንዳልፈተን ጠብቀኝ፤ ምስጋና ይብዛልህ፣ አምልኮ ይብዛልህ፤ ሁሉ ከእግርህ በታች ይንበርከክ  ምስጋና ላንተ ብቻ ይሁን ፡፡ልንል እንችላለን ፡፡
ሁለተኛው የፀሎት ክፍል ኑዛዜ ነው ፡፡ ኃጢያቱን የሚናዘዝ ይለማል የሚሸሽጋት ግን ይጠፋል  እንደተባለ ኃጢያትን መናዘዝ፤ ላጠፉት ጥፋት ኃላፊነትን መውሰድ፣ ኃጢያትን መተውና ደግሞ ላለማድረግ መወሰን የእዉነተኛ መጸጸት ወሳኝ  ክፍሎች ናቸው ፡፡ በፀሎትም ሁል ጊዜ በእግዚአብሔር ፊት መናዘዝና የኃጢያት ይቅርታ መጠየቅ የክርስስቲያንዊ ኑሮ የእለት ተእለት ክንውን ነው፡፡
 ሦስተኛው የፀሎት ክፍል ልመና ነው ፡፡ ልመና በሁለት ይከፈላል ፡፡ የመጀመሪያው ከላይ ለተናዘዝነው ኃጢያት ይቅርታ መለመን ነው፡፡ለምሳሌ ፡- አባት ሆይ ኃጢያቴና በደሌ እጅግ ብዙ ነው አሁን በዚህ ሰዓት እንኳን በፊትህ ቆሜ ብዙ በድያለሁ ፡፡ የማልወደውን ነገር እያደረግሁ የምወደውን ነገር ለማድረግ አቅቶኛል እባክህ አለማመኔን እርዳው ምህረትህን ተስፋ አደርጋለሁ፣ ይቅርታህን ፣ አባትነትህን ፣ ፍቅርህን ፣ አይተህ ይቅር በለኝ ፡፡  ማንም በፊትህ ንጹህ አይደለም ፤ ከሁሉ ደካማ ነኝ አንተ ይቅር ካላልከኝ ምንም አይወደኝም ወደየትስ እሄዳለሁ ፡፡ የላየን ሳይሆን የውስጤን ፣ የአፊን ሳይሆን የልቤን የምታውቅ በፊትህ ራቁቴን ሆኛለሁና ፈራሁ እባክህን ይቅርታህን ስጠኝ ፡፡ ስለ ስህተቴ ሰበብ የለኝም ሁሉን ወድጄና ፈቅጀ አድርጌያለሁ ኃጢያቴን አምናለሁ ጌታ ሆይ ይቅር በለኝ፡፡ልንል እንችላለን፡፡                                                                                                                                    .            ሁለተኛው ደግሞ በእለቱ በእግዚአብሔር ፊት ይዘነው ለቀረብነው ርዕሰ ጉዳይ ላይ በአምላካችን ፊት ልመና የምናቀርብበት ክፍል ነው፡፡ጸሎት በርዕስ ነው ሚጸለየው፡፡አንዳንድ ጊዜ በአንድ ሰዓት ስለ ብዙ ነገር ስለምንለምን ለጸሎታችን መልስ ተሰጥቶን እንኳን ያገኘነው መልስ በህይወት አጋጣሚ የመጣ እንጅ የጸሎታችን መልስ ላይመስለን ይችላል ፡፡ስለዚህ ወደፊት እግዚአብሔርን ለማመሰገኛም ተጨማሪ ምክንያት ይሆን ዘንድ ልመናችንን በርዕስ በርዕስ መለየት ያስፈልጋል ፡፡የፀሎታችንም አይነት እንደያዝነው ርዕስ የተለያየ የሆናል፡፡ለምሳሌ፡- የእለቱ የጸሎት ርእሳችን ፈውስ ስለማገኘት ቢሆን እንዲህ ልንል እንችላላን፤- አምላኬና አባቴ እግዚአብሔር ሆይ የመኖሪያ መንገዶች ሁሉ አዳሽ የተሰበሩ አጥንቶቸን ሁሉ የምትጠግን ስምህ መድሀኒት፣ ቃልህ መድሀኒት፣ መጎናፀፊያህ መድሀኒት የሆነ ዛሬ ወደ ህይወቴ ወደ ድካሜ ወደ ህመሜ እንድትመጣ እለምንሃለሁ፡፡ መጻጉን የፈወሰን፤አልአዛርን ከመቃብር የቀሰቀሰውን፤12  ዓመት ሙሉ ደም የፈሰሳትን ሴት ደም ቀጥ አድርጎ ታሪኳን የለወጠውም ድምጽህን አሰማኝ፡፡
አራተኛውና የመጨረሻው የፀሎት ክፍል ዲያብሎስን መቃወምና መገሰጽ ነው ፡፡ ዲያብሎስን ተቃወሙት እርሱም ከእናንተ ይሸሻል ወደ እግዚአብሔር ቅረቡ ያከብራችኋል እንደተባለ፤ በስሙ መቃወምና መገሰጽ ያስፈልጋል ፡፡ ለምሳሌ፡-በፊታችን ያለ የክፉ ሰወች ሃሳብና የሰይጣን አሰራር ሁሉ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከመንገዳችን ይወገድ፤የጠላት ምክሩ ይፍረስ፤ሙዋረተኛ አስማተኛ ጠንቋይ ሴራው ሁሉ የአኬጦፌ መክር ይሁን፤እግዚአብሔርን የሚቃወሙ ሁሉ  ይበተኑ ሰማጠራራቸው ይጥፋ፡፡እግዚአብሔርም ለጆቹን ከአጋንንት አስራር ሁሉ ለዘለአለም ይታደጋል አሜን፡፡በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፡፡ልንል እንችላላን፡፡፡
በመጨረሻም አባት ሆይ ጸሎታችንን ስለሰማከን እናመሰግንለን፤፤ምስጋና ይሁን አንድ አምላክ ለሚሆን ለአብ ለወልድ  ለመንፈስ ቅዱስ ዛሬም ዘወትርም ለዘለአለም፡፡አሜን!!!በማለት ጸሎታችንን ልናጠናቅቅ እንችላላን፡፡                                                                   ማሳሰቢያ፤-ለምሳሌ ተብለው የቀረቡት ጸሎቶች ለምሳሌየቀረቡናቸው፡፡                                                                                                                                       
እባክዎ ሌሎችም ሸር በማድረግ አገልግሎቱን በማዳረስ የበኩልወን ይወጡ፡፡

Thursday, September 25, 2014



         

               መስቀል
መስቀል ማለት የተመሳቀለ ማለት ሲሆን መስቀያ፣መሰቀያ ፤ማሰቃያ የሚል ተያያዥ ትርጉሞችን ይሰጣል ፡፡
           ጥንታዊያን ነገስታት የሞት ፍርድ የተፈረደባቸውን ወንጀለኞችና ህግ ተላላፊዎችን በተለያየ መንገድ እንዲገደሉ ያደርጉ ነበር፡፡ ለምሳሌ ባቢሎናውያን ሰዎችን እሳት በሚነድበት ጉድጓድ እየጨመሩ አሰቃይተው ሲገሉ ዳን 31-30 ፋርስና ሚዶኖች ደግሞ አናብስት ወደ ታሰሩበት ጉድጓድ ወንጀለኛውን በመመርመር ተሰባብሮ እንደሞተና ለአውሬ እራት እንዲሆን ያደርጋሉ ዳን 6÷1–28 አረቦች በሰይፍ በመቅላት ሲያስወግዱ አይሁዶች ደግሞ በድንጋይ በመውገር ይገድላሉ፡፡ ዘዳ21÷21 ዮሐ.8÷1-11 ኢያ.10÷26
     በጥንት ዘመን ከነበሩት ገናና መንግስታት አንድ የሆነውና ዓለም በታሪክ ከተመለከተቻቸው ታላላቅ ኢምፓየሮች ግንባር ቀደም የሆነው የሮማ ኢፓየር ደግሞ በህግ የተፈረደባቸውን ወንጀለኞች በእንጨት መስቀል በመስቀል እንዲሞቱ ያደርግ ነበር፡፡ በመሆኑ ጌታችን ኢየሱስ በእንጨት መስቀል ተሰቅሎ እንዲሞት የተፈረደበት በአይሁድ ህግ ሳይሆን የጊዜው የመላዋ እስራኤል ገዥ በነበሩት ሮማውያን ወንጀለኛን በሚገሉበት መንገድ ነው ፡፡
     ከክርስቶስ ልደት በፊት አምስት ዓመት ቀደም ብሎ በይሁዳ ብቻ ከሁለት ሺህ በላይ ሰዎች በመስቀል ተሰቅለው እንዲሞቱ እንደተደረገ የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ ፡፡ ከክርስቶስ ልደት በኋላ 60. አካባቢ እንኳን ከሦስት ሺህ በላይ ሰዎች በመስቀል ተሰቅለው ተገድለዋል ፡፡
     ክርስቶስ በተሰቀለበት ዘመን አራት አይነት የመስቀያ አይነቶች ነበሩ፡-
1.     2.      3. x    4.   1                                                                           ክርስቶስ  የተሰቀለው ግን በመጀመሪያው ወይም የመደመር ምልክት በሚመስለው ነው ፡፡
በጊዜው ሰው በመስቀል ተሰቅሎ እንዲሞት ሲፈረድበት ባብዛኛው የሚከተሉት ነገሮች ይፈፀማሉ -
1.   የሚሰቀል ከሆነ አይገረፍም በክርስቶስ ላይ ግን ሁለቱም ተፈፅመዋል ማቴ. 27÷26
2.   የመሰቀያ መስቀሉን እንዲሸከም ይደረጋል ዮሐ.19÷17
3.   ከከተማ ውጭ እንዲወጣ ይደረጋል፤ ዮሐ.19÷20
4.   በምስማር ተቸንክሮ ወይም በገመድ ታስሮ እንዲሞት ይደረጋል ፡፡ ክርስቶስን በገመድ እጆቹ መጋጠሚያ ላይ ካሰሩት በኋላ በምስማር መዳፉንና እግሮቹን ቸንክረውታል፡፡
5.   በመስቀሉ ጫፍ ላይ የተሰቀለበት ምክንያትና የፈጸመው መንጀል ይፃፋል፤ ኢየሱስን ለሞት የሐሰት ክስ የአይሁድ ንጉስ ነኝ ብሎ ቄሳርን ተቃውሟል የሚል ስለ ነበር ... ( ኢየሱስ ናዝራዊ ንጉሰ አይሁድ) የናዝሬቱ ኢየሱስ የአይሀድ ንጉስ የሚል የስላቅ ጽሁፍ በመስቀሉ አናት ላይ በላቲን በግሪክ በዕብራይስጥ ቋንቋ ጽፈው ሰቅለው ነበር ዮሐ.19÷19 ቆላ. 2÷14-15
6.   የስቃይ ማደንዘዥ መጠጥም ለሚሰቅሉት ይሰጥ ነበር፤ የስቃይ መጠጡን በኢየሩሳሌም የነበረው የሴቶች መሀበር ያዘጋጀው ነበር፡፡ ዮሐ.19÷23 ለዚህ ተግባራችው በምሳሌ 6÷31 ያለውን ሀሳብ እንደ መነሻ ይጠቀሙበት እንደነበር የአይሁድ ታሪክ ጸሐፊዎች የስረዳሉ ፡፡
7.   በመስቀል ተሰቅሎ እንዲሞት የተፈረደበት ሰው ደሙ ስለማይፈስ ባብዛኛው ከሁለት እስከ ሦስት ቀን ሳይሞት ሊቆይ ይችላል የሚሞተውም  በልብ ድካም ተሰቃቶ ነበር ፡፡ ሰዎች ስቃዩን አይተው እንዳያወርዱት በወታደሮች መስቀሉን ያስጠብቁ ነበር ፡፡ አልሞት ብሎ ብዙ ከቆየ ግን የቋንጃ አጥንቶቹን ሰብረው ይገላሉ፡፡ በክርስቶስ ግን ይህንን አላደረጉም በጦር ወጉት እንጂ፡፡ በነቢዩ ከአጥንቱ አንዲት አልተሰበረም ተብሎተ ነግሮዋልና፡፡ ዮሐ.19÷31-34   ማር. 15÷44
8.   በሰንበት ሰው አይሰቀልም ነበር ከሰንበት በፊትም የተሰቀለ ካለ ሰንበታቸውን እንዳያረክስባቸው ሰንበት ከመግባቱ በፊት በተለያየ መንገድ ቶሎ እንዲሞት ያደርጉና ይቀብሩታል፡፡ ዮሐ.19÷31-37
9.   የተሰቀለውን ሰው ልብስ ወታደሮች ይካፈሉት ነበር ፡፡ ዮሐ.19÷23
        ታሪካዊ ዳራውና በጊዜው በተለይም ጉታ ኢየሱስ በተሰቀለበት ወቅት የነበረው ሁኔታ ከላይ በዝርዝር ያየነውን ይመስላል ፡፡ በክርስትና የእምነት ጉዞ መስቀል ዋና ውና ማዕከላዊው ስፍራ ነው ፡፡
     በጽንስ ሀሳብ ደረጃ መስቀልን በሦስት ከፍለን ልናየው እንችላለን ፡፡
1.   እፀ መስቀል ( የእንጨት መስቀል)-ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀል ከእርጥብ እንጨት የተሰራ መስቀል ነው፡፡
                ይህ መስቀል ክርስቶስ ከተሰቀለበት ብኋላ ቅዱስ መስቀል ተብሎ ተጠርተዋል ፡፡ በክርስቶስ በግራና በቀኝ የተሰቀሉት ወንበዴዎችም እንዲሁ በእንጨት መስቀል ተሰቅለዋል ፡፡ ዋናው ቁም ነገር ግን የተሰቀሉበት የቁሳቁስ አይነት እንጨት ወይም ብረት መሆኑ ሳይሆን የተሰቀለበት ማን ነው የሚለው ነው ፡፡ የሽፍቶችን መስቀል የሽፍታ ካልን የክርስቶስን ደግሞ የመድሃኒታችን ነው እንላለን፡፡ከክርስቶስም የተነሳ የተሰቀለበት መስቀል የተቀደሰ መስቀል እንለዋለን ፡፡በክርስቶስ የሚያምን እያንዳንዱ አማኝና የእምነት ህብረት እንደ ነፃነት ምልክት ይቆጥረዋል ፡፡ ከጌጥነትም ባለፈ የእምነት ምስክርነት ነው ፡፡ መስቀልን ስንይዘው ስንነቀሰው ወይም ስንስመው በዚህ መስቀል ተሰቅሎ ባዳነኝ አምናለሁ ብሎ የልብን እምነት በአፍ እንደ መመስከር ነው ፡፡ ይህ ተውፊት በተለይ በምስራቃዊያን አቢያተ-ክርስቲያናት የተለመደ መንፈሳዊ ውርስ  ሲሆን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ለየት ያለ ስፍራ አለው ፡፡ የሰላም የእርቅ የፍቅር የነፃነት ፣የበረከት፤የጸሎት መጀመርያ፤ የድል ምልክት(ትዕምርት) ነው  አአትብ ገጽየ ወኩለንተየ በትዕምርተ መስቀል እንዲልየዘወትር ጸሎት፡፡

2.  መከራ መስቀል ( የክርስቶስ) -     በኢሳ 53÷1-ፍም   ስለ መተላለፋችን ቆስለ ስለ በደላችን ወደቀ በእርሱ ቁስል እኛ ተፈወስን ተብሎ አስቀድሞ በነቢይ እንደተነገረ የባሪያ መልክ ወስዶ፤ ከመላዕክት እንኳን አንሶ የሁላችንን ተግሳፅ ተቀብሎ ክርስቶስ አድኖናል ገላ 61 ብርቱ ዋጋም ተከፍሏል፡፡ ይኸ የዲያብሎስ አሰራር የፈረሰበት ጥል ከመንገድ የተወገደበት የክርስቶስ መከራውና ስቃዩ መስቀል ይባላል ፡፡ የተሰቀለበት መስቀል ለመዳናችን ማስታወሻ ምልክት ሲሆን መከራው፣ስቃዩና የደሙ መፍሰስ ግን ሕይወት ያገኘንበት፤ ጌታ ኢየሱስ  ስለ ኀጢያታችን ማስተስረያና ቤዛ ሆኖ የተሰጠበት ፤ታሪካችን የተቀየረበትና የእግዚአብሔር መለኮታዊ ዓላማ የተፈጸመበት የጽድቅ መንገድ ነው፡፡ ፡፡ በእርግጥም ኃጢያታችንን ለዘላለም ያስወገደበት በስቃይ እያማጠ ለክብር እኛን የወለደበትና ያዳነበት መስቀል መከራው ነው ፡፡ በመስቀሉ ጥልን ከመንገድ ጠርቆ አስወገደው እንደተባለ ይኸ ጥል የተወገደው በደሙ ፈሳሽነት በሞቱ፤ በመቃብሩና በትንሳኤው ነው፡፡ ስለሆነም የተሰቀለውን ደግሞም የተነሳውን ክርስቶስን እንሰብካለን፡፡ 1ኛቆሮ. 1÷17-25 ይህንን ጽሑፍ የምታነቡ ሁሉ የሚከተሉትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን በትኩረት እንድታነቧቸው አሳስባለሁ ፡፡ 1ኛቆሮ. 1÷17-25 ፊሊ.2÷5-ፍም ቆላ. 1÷19-20 ኤፌ.2÷14-16 ሮሜ 3÷25 ገላ.3÷13 ሮሜ 6÷1-11 ገላ.2÷15-20 ገላ.2÷24  ገላ.6÷14
·         ትኩረት፤- ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሳለ የተናገራቸው ሰባቱ የመስቀል ቃላት በሀዲስ ኪዳን የመዳን ትምህርት ውስጥ ከፍተኛ ትርጉም የሚሰጣቸውና ከክርስቶስ የቤዛነትና የአርአያነት ስራ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያላቸው ናቸው ፡፡ ሰፊ ዝርዝር ስለሚያስፈላጋቸው ዛሬ መነካካት ባያስፈልግም የሚገኙበትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ልጠቁማችሁና በየግላችሁ እንድታጠኗቸው ደግሜ አሳስባለሁ ፡፡ በሌላ ጊዜ እግዚአብሔር ቢፈቅድ ምንአልባትም በሰሞነ ህማማት አካባቢ በዝርዝር የምንመለስባቸው ይመስለኛል ፡፡ 1. ሉቃ 23÷34 2. ዮሐ.19÷25 3. ሉቃ. 23÷43 4. ዮሐ.19÷28 5. ዮሐ.19÷30 6. ሉቃ. 23÷46 7. ማቴ. 27÷46

3. የክርስቲያን መስቀል
           ጌታ በወንጌል እያንዳንዱ መስቀሉን ተሸክሞ ይከተለኝ ነፍሱን ያተርፋል ማቴ.10÷24-25   በማለት ለደቀ መዛሙርቱ ባስተማረበት በመዋዕለ ሥጋዌው በአንዱ ቀን ሁሉ ሊሸከመው የሚገባ የራሱ መስቀል እንዳለው አስገንዝቧል ፡፡ መስቀሌን ተሸክሙ ብሎ ቀንበር አልጫነብንም የእርሱን መስቀል ልንሸከም አንችልምና፡፡አቅም የለንም፡፡ ደግሞም እርሱ የመጨረሻውን የመስቀል አገልግሎት አንዴ ለዘለዓለም ፈፅሞታልና የክረስቶስን መስቀል ዳግም መሸከም አይቻልም አያስፈልግምም ፡፡የሚያፈልገው አንድ ነገር ቢኖር በተሰቀለው ማመን ነው፡፡ የሚያምኑት ግን የሆሳዕና ለመዘመር ብቻ ሳይሆን በሞቱም ለመተባበር ስለተጠሩ ሮሜ 61 በህይወት ውጣ ውረድ በአንድም በሌላም መንገድ የየራሳቸውን መስቀል  ይሸከማሉ፤ ፊሊ.1÷29 የተጠራነው አመኖ ለመኖር ብቻ ሳይሆን አመኖ ለመሞትም ነው፡፡ከባዱ ነገር አመኖ መኖር አይደለም፡፡ዕብ 1113
አማኞች ወደዚህ ህይወት የገባነው አስቀድሞ ተነግሮን ነው፡፤እኔን የተከተለ መከራ አለበት ተብሎ ልዩነቱ የአማኞች ፈተና የሚመጣው መውጫውን ይዞ ነው ፡፡በመጀመሪያ በማንም ላይ ሆኖ የማያውቅ ፈተና በእኛ ላይ አይሆንም ደግሞም ከምንችለው በላይ የሆነ መከራ እንድንሸከም ተላልፈን አንሰጥም ይመጣ ዘንድ ያለው ቢመጣ እንኳን ፈተናው ከመውጫው ጋር ተዘጋጅቶዋል፡፡ከሁሉም በላይ ግን በእግዚአብሔር ለሚያምኑ እንደ ሳቡ ለተጠሩ ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን፡፡፡1ኛቆሮ.10÷10  ሮሜ 828 የትም ቦታ መስቀል  ( መከራ፣ ፈተና ) አለ ፡፡ መከራው ላይቀር ዋጋ የሚያስጥ መከራ መቀበል ብልህነት ነው ፡፡ የእግዚአብሔር በረከት ያለው በመከራ ወረቀት ተጠቅሎ ነው ፡፡ የኤርትራን ባህር ሳይሻገሩ፤ በሲና በርሃ ሳያልፍ፣ በቃዴስ በርኔ ረሃብና ጥም ሳይፈራረቁብን ከንዓን አንገባም ፡፡ ወርቅ ወርቅ የሚሆነው በእሳት ተጠብሶ ነው ፡፡ እሳት አልፈልግ ካለ ግን ጭቃ ሆኖ መኖር ይችላል የምርጫ ጉዳይ ነው፡፡ በአማኞች ህይወት ፈተና በተለያየ ምክንያት ከተለያየ ቦታለመጣ ይችላል ፡፡
1.   ከሰይጣን የሚመጣ ፈተና - ይህ ዓይነቱ ፈተና እግዚአብሔርን አስከብረን መንፈሳዊ ተጋድሎ በመፈፀም የተዘጋጀውንም የድል አክሊል ለመቀበል የሚያበቃ በእምነት የምናድግበትና የምንነጥርበት መንፈሳዊ ትግል ነው ፡፡ በነገራችን ላይ በሰይጣን የሚፈተን ሰው የመንፈሳዊነት ደረጃው ላቅ ያለ ራሱን በራሱ ከመፈተን ያለፈ የሰዎችን ፈተና ያሽነፈ በአብዛኛው ሶስተኛው የመንፈሳዊ እድገት ላይ ( ፍፁምነት ) የደረሰ አማኝ የሚገጥመው አይነት ውጊያ ነው ፡፡
                መቼም ሰይጣን ጡረታ የማይወጣ ጠላት ነው ፡፡ የዘላለም ሀሳቡ የሰውን ዘር ሁሉ ማጥፋት ነው ፡፡ እርሱ ከጥንት ዘመን ጀምሮ ነፍስ ገዳይ እንደሆነ ቅዱሳት መጽሐፍት ይመሰክራሉ ዮሐ 844 ዘፍ 31-8 ፡፡ በኢዮብ ህይወት እንዳየነው ልጆቹን ከገደለ ሀብትና ንብረቱን አጥፍቶ እንኳን ስላልበቃው ሰውነቱን በቁስል መትቶ ፤ጓደኞቹ እንዲተውትና ሚስቱ እንድትጠላው አድርጎ እጅግ ፈተነው፡፡ ሰውነቱን ቆራርጦ ምላሱን ብቻ ተወለት ምላሱን የተወለትም ለኢዮብ አዝኖ ሳይሆን ስቃዩ ሲበዛበት እግዚአብሔርን ይሰድብልኛል ብሎ ስላሰበ ነበር ፡፡ ኢዮብ በእምነት እንደበረታ፣ በፈተናም እንዳልዛለ ባወቀ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ልጆች ጉባኤ ሔዶ የኢዮብን ነፍስ ለመነ ፡፡ እግዚአብሔር ግን በልጆቹ ነፍስ ፈጽሞ አይደራደርምና የኢዮብን ነፍስ ከለከለው ፡፡ ሰይጣን የሚፈልገው ገንዘባችንን፣ልጆቻችንን ወይም ሌላ ሌላውን ነገራችንን ሳይሆን ህይወታችንን ነው ፡፡ የእግዚአብሔር ሰው አብርሃምም በልጁ በይስሃቅ ህይወት ነበር የተፈነው፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር ሰይጣን መወራረድ የፈለገው በቅዱሳኑ ነፍስ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ግን ከፃድቃኖቹ ጋር ስለ ነበር የእግዚአብሔር ቅዱሳን ሁሉ በፈተና ነጥረው ወጥተው አክሊላቸውን ተቀብለዋል ፡፡
           እንደሚታወቀው ሰይጣን 7500 ዓመት በላይ የመፈተን፣የመጣል፣የመግደል ልምድ ያለው ባላጋራ ነው፤ ፍላጎታችን ውስጥ መሽጎ ከህሊናችን አጣልቶ ሲያሰቃየን ይኖራል ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ጥላችን ከሥጋና ከደም ጋር አይደለም  ከርኩስ መንፈስ ከከክፋት ሁሉ ሰራዊት ጋር ነው በማለት  የጦርነቱ ሁኔታ መንፈሳዊ መሆኑን ያስገነዘባል ፡፡ በመንፈሳዊ ውጊያ ደግሞ እንደ አቶሚክ ወይም ኒውክለር መሳሪያ ከባድ የማሸነፊያ መንገዶች ፆምና ፀሎት ናቸው፡፡ ጌታም በወንጌል እንዲህ ያለው ጋኔን ከፆምና ከፀሎት በቀር አይወጣም እንዳለ ፡፡ ስለሆነም ይህንን የጥፋት ሁሉ አባት ፤የርኩሰት ሁሉ እናት ማሸነፍ የምንፈልግ ከሆነ ከልማድ ፆና ፀሎት በተለየ መልኩ በሱባኤና በጽሞና በእግዚአብሔር ፊት መውደቅ ያስፈልጋል ፡፡ ሰይጣን የማይሸነፍ ጠላት አይደለም ተቃወሙት እርሱም ከእናንተ ይሸሻል ተብሎ ነው የተፃፈው ፡፡ አንዴ ተጥሏል የተጣለውን በእምነት መርገጥ ለአማኞች የተሰጠ የልጅነት ስልጣን ነው ፡፡ ዮሐ.1÷12 እምነት ደግሞ ምልክቶች ይከተሉታል፤ አጋንንትንም ያሸንፋል፤ የማንችለውንም ያስችላል ፡፡ማር 1616
2.   ከሰው የሚመጣ ፈተና - ክፉ ሰዎች በሦስት ይከፈላሉ ይባላል፡፡ ሰይጣን ያደረባቸው፤ ሰይጣን የሚያማክራቸውና ፍፁም ሰይጣን የሚመስሉ፡፡ ትልቅ ፀሎት ማለት ከእነዚህ ይጠብቀን ማለት ነው ፡፡ በቀላል ምሳሌ ለመረዳት በነብየ እግዚአብሔር ንጉስ ዳዊት ህይወት ውስጥ ተከሰተው የነበሩ ሁለት ፈተናዎችን እናንሳ ሀሳቦች ለማግኘት እንሞክር
            የመጀመሪያው የዳዊት ፈተና ጎልያድ ነው ሁለተኛው ሳኦል ነው ፡፡ ሳኦል የሚሸሸው ፈተና ሲሆን ጎልያድን ግን የግድ መጋፈጥ አለበት ፡፡ ምክንያቱም በጎልያድና በዳዊት መካከል ያለው ጦርነት ስለ እግዚአብሔርና ስለ ህዝቡ የመጣ ፈተና ነው ፡፡ የእስራኤልን ቅዱስ እየተሳደበ የመጣውን እስራኤልን ሊያጠፋ የሚፈልገውን ጎልያድን ከመጋፈጥ ውጭ ለዳዊት ምንም ምርጫ የለውም ፡፡ በቃ መጋፈጥ ነው ተጋፈጠው፡፡ ሳኦልን ግን መሸሽ መንፈሳዊነት ነው ምክንያቱም የሳኦል ችግር የዝና፣የገንዘብ፣የስልጣን፣የዙፋን ነው ፡፡ ሳኦል እንዲሁ ይለፋል እንጂ ዳዊት መንገሱ አይቀርም ስለዚህም ዳዊት ዘወር አለ፡፡ ከመጋፈጥም የእግዚአብሔርን ጊዜ መጠበቅ እንደሚሻል አመነ ብቻውን ዋሻ ውስጥ በጨለማ ስፍራ አግኝቶት እንኳን ሊገድለው አልፈለገም ሌሎቹንም ከለከለ እንጂ፡፡
           ይሄኛው አይነት ፈተና በአብቻኛው ሁለተኛው ደረጃ ላይ የሚገኙት ( ማዕከላዊያን ) ምዕመናን ላይ ተደጋግሞ የሚታይ ነው ፡፡ በክርስትና እድገት አደገኛው ደረጃ ነው ፤ወይ ፍፁም ሆኖ አልጨረሰ ወይ ወጣኒ ሆኖ ድካሙን አልተረዳ ነገሩን ሁሉ የእምነት ጉዞውን ጨምሮ ከሰዎች እንቅስቃሴ ጋር እያስተያየ የሚተገብርበት ፤ሲወድቁ የሚወድቅ፤ ሲነሱ የሚነሳ ፤ከብዙ ሰዎች ጋር ግጭት ውስጥ የሚገባ በሰዎች አብዝቶ የሚፈተን አይነት ሰው የሚገኝበት ደረጃ ነው ፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ያለ ሰው አርቆ ማየትና የት ጋር እንደቆመ ማሰብ ካልቻለ ከእግዚአብሔር ክብር እስከ መጥፋት ሊያደርስ የሚችል ውጊያ አለው ፡፡ ለዚያም ነው ጌታ እርስ በእርሳችሁ ተዋደዱ ፣ወንድሙን ማንም አይሳደብ ፣አያሰናክል ፍርዱ ታላቅ ነው እያለ አጥብቆ ያስተማረው ፡፤እንዲያውም በእግዚአብሔር መንግስት የመጨረሻው ፍርድ የወንጀለኛ መቅጫ ያደረገው የፍርዱ ምስክርነት ቃል ይሄንኑ በሰወች መካከል የለ ግንኙነትን ነው፡፡ተርቤ ተጠምቼ በማለት በሰወች የሚሆነው ሁሉ በእርሱ እንደሆነ አድርጎ ይቀጣበታል ይባርከበታል ፡፡
            ከዳዊት ልንወስደው የሚያስፈልገው ቀጥተኛ ትምህርትና በዚህ አውድ ትኩረት የሚሰጠው ዋና ሀሳብ ስለ እግዚአብሔር ክብርና ለቅዱሳኑ አንድ ጊዜ ስለተሰጠው ሃይማኖት መንፈሳዊ ትግል እንድንታገል ሲያስገነዝብ ነገር ግን ስለ ምድራዊ ክብር የሆነውን ማንኛውም ነገር ንግስና ቢሆን እንኳን እንድንሸሸውና እንድንፀየፈው ያስገነዝበናል ፡፡
3.   ከራስ የሚነሳ ፈተና - የሰው ጠላቱ ራሱ ነው ይላል ያገራችን ሰው ፡፡ በመንፈሳዊ ህይወት በተለይ ጀማሪ ( ወጣኒ ) የመጀመሪያው ደረጃ ክርስቲያን እያለን እጅግ አስቸጋሪው ነገር ከፍላጎትና ከስሜት የሚነሳው በመመኘት ምክንያት ሞትን የሚወልደው ኃጢያት ነው ፡፡ ያዕ.1÷12-15 ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ጉዳይ ሲገልጥ ስጋ በስጋ ህግ ፤መንፈስ በመንፈስ ህግ ይስበኛል ፡፡ የማልወደውን አደርጋለሁ የምወደውን አላደርግም በማለት የስጋ ድካምና የኃጢያት ጉልበት በሰው የእለት ተእለት እንቅስቃሴ ውስጥ ምን እንደሚመስሉና ለመቆጣጠር ምን ያህል አስቸጋሪም እንደሆነ አስረድቷል ፡፡በርግጥም የጳውሎስ ህይወት ይህንን  ያህል ከፈተነው ከብዙመቻችን አንጻር ሲተይ ቀላል አይሆንም፡፡ ብዙ ጀግኖች ፣የተወደዱና የተከበሩ ሰወች፤ አገር መሪወችና ዝነኞችና የእግዚአብሔር ሰዎች ሳይቀሩ ከውስጥ በሚነሳ ማእበል ተሰናክለው ወድቀዋል፡፡እሰክ አስቡት አንድ ሰው ሲፈቀር የሚንቀባረረውን ያህል ሲያፈቅር እንደዛ መሆን የሚችል ይመስላችኋል  አይችልም ፡፡ከራሱ የተነሳ ፈተና ነውና፡፡
         አንድ አይነተኛ ለአብነት የሚሆን ታሪክ ደግሞ ከቅዱስ ዳዊት ህይወት እሁንም እንምዘዝ፣ የእግዚአብሔር ልብ የተባለው ዳዊት ጎልያድን ገሎ ሳኦልን ታግሶ እግዚአብሔር ካነገሰው በኋላ ቤርሳቤህ የምትባል ፈተና ስሜቱን ቀስፋ ያዘችው ሁሉን የረታው ዳዊት ልቡን መርታት አልቻለም ፤ሁሉን ያሸነፈው ዳዊት ስሜቱን ማሸነፍ አልቻለም፡፡ ቤርሳቤህን ወሰደ ረከሰ ፤ኦሪወንን አስገደለ በዚህ ምክንያት 70ሺህ እስራኤላውያን አለቁ፡፡
ራስን መግዛት ከመንፈስ ስራዎች አንዱና መሰረታዊ ከሚባሉት የሚጠቀስ ነው ፡፡ በርግጥ ራስን መግዛት አገር የመግዛት ያህል ቀላል አይደለም ፍላጎት ንጉስ በመሆንና  በጦር ሰራዊት ብዛት አይቆምም፡፡ ኑሮ ሒደት ነው አሁን ያለውን ማንነታችንም የተቀረጸው በሂደት ነው እኛነታችን ውሎ፣ትምህርት፣ዕድሜ፣ውድቀት፣ጓደኛ፣ቤተሰብበ በየጊዜው ውስጣችን ካስቀመጡት መልካምም ይሁን መጥፎ ነገር በመነሳት የዳብረው ስብዕና ነው ፡፡ ሁለችንም በሰለን ከሆነ የበሰልነው እንጨት ጨርሰን ነው፡፡በሂደት በእግዚአብሔር ርዳታ እንድ  ቀን ወደሚፈለገው  መንፈሰዊነት መድረሳችን አይቀርም ፡፡ስለዘህ ሰይጣን ዕድል እንዳያገኝና ሕይወታችንን እንዳይቆጣጠር  መጀመሪያ ደከማ ጎናችንን ለይቶ ማወቅ ከዘያም ተረጋግቶ ከችግሩ መውጣት ደግሞም ወደዚያው ላላመመለስ  መትጋት ይገባል፡፡ ለመንፈሳዊ ሰው ግን ራስን ከማሸነፍ የሚበለጥ ድል የለም ፡፡ በመነኮሳት መጽሐፍ አንድ ታሪክ ተጽፎአል ሁለት መነኮሳት በመንገድ ሲያልፉ ጥቅል ወርቅ ወድቆ አገኙ ፡፡አንዱ ለመነኩሴ ገንዘብ ምኑ ነው ብሎ አልፎት ሔደ አንዱ ደግሞ መልካም ስራ ብሰራበት መልካም እንጂ ብሎ አንስቶ ብዙ ድሆችን እየመገበ፣ አረጋውያን እየጦረ፣እጓለማውታን እየተንከባከበ ኖረ፡፡ ከብዙ ዘመን በኋላ እግዚአብሔር ለሁለቱም እኩል ክብር ሰጣቸው ፡፡ ገንዘብ ወሰዶ መልካም ስራ የሰራበት መነኩሴ እግዚአብሔርን ጠየቀ ለእኔ ይኸ አይገባኝም ይኸንን ሁሉ ሰርቸ ጓደኛየ ምን ስላደረገ ነው ከእኔ እኩል አለ ፡፡ ጌታም ያኔ ገንዘቡን ንቆ ራሱን ተቆጥሮ ሲያልፈው አንተ አሁን የደረስክበት ክብር ደርሶ ነበር አለው ፡፡    ስሜታችን የሚገዛን ሳሆን ሥሜታችንን የምንገዛ ያድረገን፡፡አሜን፡፡፡፡፡፡
  
መልካም ምንባብ


እባክዎትን ለሌሎች ሸር ያድርጉ !!!!